የአማራ ገጠር መንገደች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ዋናው መ/ቤት አመራሮች እና ሰራተኞች በኤጀንሲው የ2018 ዓ.ም ዕቅድ ላይ ውይይት አካሄዱ።
የኤጀንሲው የ2018 ዓ.ም የቁልፍ እና ዓበይት ተግባራት ዓላማዎችና ግቦች እንዲሁም ዝርዝር ተግባራትን ያካተተ የመንገድ ልማት ስራዎች እቅድ በ04/13/2017 ዓ.ም በኤጀንሲው የዕቅድ ዝግጅት፣ ክትትል እና ግምገማ ደጋፊ የሥራ ሂደት መሪ አቶ ባሻ እንግዳው ቀርቦ በኤጀንሲው ዋና መ/ቤት አመራሮች እና ሠራተኞች ውይይት ተደርጎበታል።
እቅዱ በቀረበበት ወቅት ኤጀንሲው በ2018 በጀት አመት ከክልሉ መንግስት በተመደበ ከብር 1.3 ቢሊዮን በላይ በጀት በ33 ነባርና አዳዲስ ፕሮጀክቶች 102.15 ኪ.ሜ መንገድና 227 ስትራክቸሮችን ለመገንባት እና ከፌዴራል መንገድ ፈንድ ጽ/ቤት በተመደበ ከ1.2 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት በ289 የጥገና መስመሮች 6‚038 ኪ.ሜ ነባር መንገዶችን ለመጠገን በእቅድ መያዙ ተገልጿል።
በውይይቱም የተቋሙ እቅድ ክልሉ ካቀደው የ25 አመት የአሻጋሪ እድገትና ዘላቂ ልማት ፍኖተ ካርታ ከተወሰደ የ5 አመታት ስትራቴጅክ እቅድ መነሻ ተደርጎና የህዝብን የመልማት ጥያቄ ግምት ውስጥ አስገብቶ የተዘጋጀ በመሆኑ ከዚህ ቀደም ከነበረው አሰራር ወጣ ባለ መልኩ መፈፀምን የሚጠይቅና የሁሉንም አካል የጋራ ርብርብ የሚጠይቅ መሆኑ በተቋሙ ሰራተኞች ዘንድ የጋራ መግባባት ላይ ተደርሷል።

የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ቀለሙ ሙሉነህ በውይይቱ ማጠቃለያ ላይ እንደገለፁት ኤጀንሲው የመንግስትና የህዝብን ተልዕኮ የተሸከመ ተቋም በመሆኑ ከእያንዳንዳችን ምን ይጠበቃል የሚለውን በአግባቡ ይዞ መስራት የሚጠበቅ ሲሆን እቅድን፣ ሀብትንና የሰው ሃይልን በጥብቅ ዲሲፕሊን መምራት ከአመራሩ እንደሚጠበቅና ሰራተኛውም የእቅዱ ባለቤት መሆን፣ የታቀደውን እቅድ ለመፈፀም ቁርጠኛና ተነሳሽ መሆንና ስራን በጋራ፣ በቅልጥፍናና በቅንነት በመስራት እቅዱን ማሳካት እንደሚጠበቅበት አስገንዝበዋል።
የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ የበጀት ዓመቱን ዕቅድ ለመፈፀም ጥረት በማድረግ ላይ ነዉ፡፡
ኤጀንሲዉ በበጀት ዓመቱ ከክልሉ መንግስት በተመደበ 1.1/አንድ ነጥብ አንድ/ ቢሊዮን ብር ካፒታል በጀት በ39 የመንገድና ድልድይ ፕሮጀክቶች 80 ኪ.ሜ መንገድ እና 88 የተለያየ መጠን ያላቸዉ ስትራክቸሮች ግንባታ ለማከናወን አቅዶ እየሰራ ሲሆን እስከ መጋቢት መጨረሻ 2017 ዓ.ም ባለዉ ጊዜ ወደ ስራ በገባባቸዉ 36 የመንገድና ድልድይ ፕሮጀክቶች 17.37 ኪሜ የመንገድ ግንባታ በማከናወን የ9 ወሩን ዕቅድ 38.84% ፣የዓመቱን ዕቅድ ደግሞ 21.72% አከናዉኗል፡፡ ኤጀንሲዉ የበጀት ዓመቱን ዕቅድ ለመፈፀም ጥረት በማድረግ ላይ ሲሆን ባለፉት 9 ወራት የተለያየ መጠን ያላቸዉ ድልድዮች በመገንባት ረገድ የተሻለ አፈፃፀም ታይቷል፡፡ የ9 ወሩ የመንገዶች ግንባታ አፈፃፀም ግን አነስተኛ ሆኖ ይገኛል፡፡ በመንገዶች ግንባታ የተመዘገበዉ አነስተኛ አፈፃፀምም ቢሆን ፈተናዎችን ተቋቁሞ በመስራት የተመዘገበ አፈፃፀም ነዉ ፡፡
ለአፈፃፀሙ ማነስ በክልሉ በተፈጠረዉ የፀጥታ ችግር ምክንያት በሙሉ አቅም መስራት አለመቻል፣ የራስ ኃይል የግንባታ ማሽነሪ እና ተሸከርካሪ እጥረት፣የኪራይ ማሽነሪ እና ተሸከርካሪ እንዲሁም መለዋወጫ በገበያ ላይ ማግኘት አለመቻል በዋናነት ይጠቀሳሉ ::
በቀሪ ወራት በፈተና ዉስጥ ሆኖም ቢሆን የተሻለ አፈፃፀም ለማስመዝገብ ሰፊ ጥረት ማድረግ እንደሚገባ የኤጀንሲዉ የ2017 ዓ.ም የ9 ወር ዕቅድ አፈፃፀም ግምገማ ከኤጀንሲዉ ዋና መ/ቤት አመራሮች እና ሰራተኞች ጋር በተካሄደበት ወቅት ተመልክቷል፡፡
የሀዘን መግለጫ
የአማራ ገጠር መንገዶች ኮንስትራክሽን ኤጀንሲ የጉማራ- ናበጋ- ማክሰኝት ሎት 2 ፕሮጀክት ሀላፊ የነበሩት አቶ አሰፋ ስንሻው በደረሰባቸው ድንገተኛ አደጋ ህይወታቸው በማለፉ ኤጀንሲው የተሰማውን ጥልቅ ሀዘን ይገልፃል።
ለቤተሰቦቹ፣ ለጓደኞቹና ለስራ ባልደረቦቹ መፅናናትን ይመኛል።

Message From General Manager

